ኢትዮጵያ ወይም በይፋ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢ.ፌ.ዲ.ሪ.) በአፍሪካ ቀንድ የምትገኝ የረጅም ዘመን ታሪክ ያላት ሀገር ናት። በአፍሪካ ነፃነቷን ጠብቃ የኖረች ብቸኛ ሀገር ነች። በህዝብ ብዛት ከአፍሪካ ኢትዮጵያ ሁለተኛ ስትሆን ፣ በቆዳ ስፋት ደግሞ አስረኛ ናት። ዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ናት።
አብዛኛዎቹ የአፍሪካ ሀገሮች ዕድሜያቸው ከአንድ ምዕተ-ዓመት የሚያንስ ሲሆን ፣ ኢትዮጵያ ግን ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በንጉሠ-ነገሥታት እና ንግሥተ-ነግሥታት የተመራች ሀገር ናት። የሰለሞናዊው ሥርወ-መንግሥት የአመጣጡን ዘር እስከ አስረኛው ዓመተ-ዓለም ድረስ ይቆጥራል። ኢትዮጵያ የሰው ልጅ ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የኖረባት ቦታ እንደሆነች ብዙ የሳይንሳዊ መረጃ ተግኝቷል። በበርሊን ጉባኤ በኩል የአውሮፓ ሀያላት ሀገሮች አፍሪካን ሲከፋፍሏት፣ ኢትዮጵያ ነፃነቷን ጠብቃለች። የሊግ ኦፍ ኔሽንስ (League of Nations) አባል ከነበሩት ሶስት የአፍሪካ ሀገሮች አንዷ ነበረች። ከአጭር የኢጣልያ ወረራ ጊዜ በኋላም ከየተባበሩት መንግሥታት መሥራቾች አንዷ ናት። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት ነፃነታቸውን ሲያገኙ፣ ሰንደቅ-አላማቸውን በኢትዮጵያ ቀለሞች ማለትም በአረንጓዴ ፣ ቢጫ እና ቀይ ላይ ነው የመሠረቱት። አዲስ አበባ ደግሞ ለየተለያዩ በአፍሪካ ላይ ላተኮሩ አለም አቀፍ ድርጅቶች መቀመጫ ሆነች።